የ2007 ረቂቅ በጀት
እንደ ሚኒስትሩ ማብራሪያ በ2007 በጀት አመት የ11 ነጥብ 4 በመቶ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እድገት እንደሚመዘገብ ታሳቢ የተደረገ ሲሆን፥ የአንድ አሀዝ የዋጋ ንረት እንደሚኖርም ይጠበቃል። የእቃዎች የሀገር ውስጥ ገቢ በ20 ነጥብ 5 በመቶ እንዲሁም የወጪ ገቢ 13 ነጥብ 1 በመቶ እድገት እንደሚያሳይ ታሳቢ መደረጉን የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትር አቶ ሱፊያን አህመድ ገለፁ።
የ2007 ለፌዴራል መንግሥት መደበኛና ለካፒታል ወጪ፣ ለክልል መንግሥታት ድጋፍና ለምዕተ ዓመቱ የልማት ማስፈፀሚያ የሚውል 178 ቢሊዮን 565 ሚሊዮን 906 ሺህ 571 ብር ተደግፎ ቀርቧል። ይህም ከ2006 በጀት አመት ጋር ሲነጻጸር በ15 ነጥብ 3 በመቶ ብልጫ ያለው ነው።
ከሀገር ውስጥ ገቢና የውጭ እርዳታ 157 ቢሊዮን 357 ሚሊዮን 943 ሺህ 657 ብር ለማግኘት ታቅዷል። በዚህም መሰረት 21 ቢሊዮን 207 ሚሊዮን 962 ሺህ 914 ብር ጉድለት ይታያል። ከሀገር ውስጥ ብድሩ ከአጠቃላይ ምርት አንፃር 1 ነጥብ 8 ብቻ በመሆኑ በዋጋ ንረት ላይ ተጽዕኖ እንደማያሳድር ታምኖበታል።
የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስትሩ አቶ ሱፊያን አህመድ የ2007 አመታዊ የፌደራል መንግስት ረቂቅ በጀትን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤቱ አቅርበዋል።
አቶ ሱፊያን ባለፉት ሶስት አመታት የተከናወኑ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ አገልግሎቶችና መሰረት ልማት ማስፋፋት ስኬታማ መሆናቸውን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አስረድተዋል።
ከ2003 እስከ 2005 የኢትዮጵያን ኢኮኖሚ የ10 በመቶ እድገት አሳይቷል ያሉት አቶ ሱፊያን፣ ግብርናው 70 በመቶ፣ ኢንዱስትሪውና የአገልግሎት ዘርፉ ደግሞ የ16.9 እና 11 በመቶ እድገት አስመዝግበዋል ብለዋል።
የነብስ ወከፍ ገቢ
ባለፉት ሶስት አመታት የዜጎች የነብስ ወከፍ ገቢ ማደጉንና በአንፃሩ ስራ አጦች ቁጥር በከፍተኛ ደረጃ መቀነሱን አቶ ሱፊያን አብራርተዋል።
የዜጎች የነብስ ወከፍ ገቢ በ2002 ከነበረበት 373 የአሜሪካን ዶላር በ2005 ወደ 550 የአሜሪካን ዶላር ከፍ ብሏል።
በ2003 ዓ.ም በተደረገ ጥናት ባለፉት ሶስት አመታት የስራ አጥነት ቁጥር ወደ 26.9 ዝቅ ማለቱን እንዲሁም ይህ ቁጥር በ2006 ዓ.ም ወደ 26 በመቶ ዝቅ ብሏል ብለዋል።
በ2005 ዓ.ም በተመዘገበው እድገት ብቻ ከ1 ሚሊዮን በላይ ዜጎች የስራ እድል ተፈጥሯልም ነው ያሉት አቶ ሱፈያን።
በከተሞች የስራ አጥነት ምጣኔ ወደ 16 በመቶ ዝቅ ብላል ነው ያሉት ሚኒስትሩ።
መሰረተ ልማት
በመጀመሪያዎቹ ሶስት የእቅድ ዘመን በርካታ የመንገድ፣ የባቡር፣ የኢንዱስትሪ፣ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ እንዲሁም የመጠጥ ውሃ ፕሮጀክቶች የተከናወኑ ሲሆን የሀገሪቱ የመንገድ ሽፋን በ2004 ከነበረው 56 ሺህ 190 ኪሎ ሜትር በ2006 ወደ 58 ሺህ 338 ኪሎ ሜትር ከፍ ማለቱንም ገልፀዋል። የገጠር አጠቃላይ መንገዶችንም እንዲሁ 27 ሺህ 678 ኪሎ ሜትር ደርሷል። ይህም ከገጠር ቀበሌዎች ወደ ዋና መስመሮች ለመድረስ የሚወስደው ጊዜ ወደ 2 ስአት ዝቅ አድርጎታል።
ጤና
እንደ አቶ ሱፊያን ገለፃ የጤናው ዘርፍ መሰረታዊ የጤና አገልግሎቶች ሽፋን 93 በመቶ ደርሷል። ሀገሪቱ የህፃናትና እናቶች ሞትን በመቀነስ እምርታ ማሳየቷን የገለፁት ሚኒስትሩ፥ የህፃናትን ሞት በ2/3ኛ በመቀነስ የሚሌኒየሙን የልማት ግብ ቀድማ ማሳካት ችላለች ብለዋል።
ትምህርት
አጠቃላይ የትምህርት ተሳትፎም በ2005 94 ነጥብ 5 በመቶ ደርሷል፤ 17.3 ሚሊዮን በላይ ህፃናትም በትምህርት ገበታ ላይ ይገኛሉ ብለዋል ሚኒስትሩ።
የሀገር ውስጥ ገቢ
አቶ ሱፊያን የሀገር ውስጥ ገቢ በየአመቱ በ36 በመቶ እያደገ መምጣቱን ገልፀው፤ ለመሰረተ ልማት ግንበታና ለድህነት ቅነሳ የተመደበው በጀት ከፍተኛውን ድርሻ እንደሚወስድ ጠቁመዋል። በበጀት አመቱ ከታክስና ታክስ ካልሆኑ ገቢዎች 96 ቢሊዮን 955 ሚሊዮን ብር ከፌደራል መንግስት የተሰበሰበ ሲሆን፥ ይህም አፈፃፀሙ 88 ነጥብ 8 በመቶ መሆኑን ያሳያል ብለዋል። ከዚህም ውስጥ ከታክስ የተገኘው ገቢ 79 ቢሊዮን 471 ሚሊዮን ሲሆን፥ በእቅዱ መሰረት ለማግኘት የታቀደውን 100 ቢሊዮን ብር ለማሳካት ርብርብ ይጠይቃል ብለዋል።
ምንጭ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት
No comments:
Post a Comment