ኢትዮጵያውያን ሽብርተኝነት የሀይማኖት ጭምብል ለብሶ መምጣቱ ሳያዘናጋቸው ሀይማኖት ሳይለዩ በአንድ ልብ እና ሃሳብ ቆመው ሊዋጉት እንደሚገባ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀይለማርያም ደሳለኝ ገለፁ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዓለም አቀፉ አሸባሪ ቡድን አይ ኤስ በኢትዮያውያን ላይ የፈፀመውን የግፍ ግድያ አስመልክተው ለኢብኮ በሰጡት መግለጫ በድርጊቱ መንግስት እጅግ ማዘኑን አስታውቀዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአሸባሪ ቡድኑ ለተሰዉ ቤተሰቦች እና በአጠቃላይ ለኢትዮጵያውያ ህዝብ መፅናናትን ተመኝተዋል።
ይህ የሰው ዘርን ለማጥፋት የተነሳን አሸባሪ ቡድን ዜጎች ከመንግስት ጎን ሆነው እንዲዋጉትም ነው ጥሪ ያቀረቡት።
“በዚህ አሰቃቂ ግድያ የኢትዮጵያ ክርስቲያኖችን ማዕከል አድርገን ገድለናል ብለው ያሳወቁን ቢሆኑም እነዚህ ኃሎች መላውን የሰው ዘር የሚያጠፉ መሆናቸውን ግንዛቤ ውስጥ አስገብተን መላው የኢትዮጵያ ሕዝቦች በየትኛውም ኃይማኖት ውስጥ ያለን አሸባሪዎችንና አክራሪዎችን መዋጋት አለብን” ብለዋል። በዚህም ወቅት ኢትዮጵያውያን በአንድ ሀሳብ እና ልብ መቆም ይገባናልም ነው ያሉት።
“በውጭ ያሉ በተለይም እንደዚህ ዓይነት አደገኛ ሁኔታ ሊፈጠርባቸው በሚችሉ አካባቢዎች ያሉ ዜጎቻችን በፈቃዳቸው ወደ አገራቸው እንዲመለሱ መንግስት ይፈልጋል ብለዋል” አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ።
መንግስት ሊቢያን ጨምሮ በየመን እና ደቡብ አፍሪካ የሚገኙ እና ወደ አገራቸው ለመመለስ የሚፈልጉ ኢትዮያውያን ለአገራቸው እንዲበቁ የሚጠበቅበትን ለማድረግ መዘጋጀቱን ነው ያስታወቁት።
ወደ አገራቸው ከተመለሱም በኋላ ተቀብሎ ያስተናግዳል ብለዋል።
No comments:
Post a Comment